በደልም ይረሳል፣ ምነው አይረሳ (ዋቻሞ)
በደልም ይረሳል፣ ምነው አይረሳ
ዋቻሞ
(“በደል ይረሳል ወይ?” ለሚለው የወለላዬ ግጥም የተሰጠ ምላሽ)
ረሃብ ቸነፈር፣ ወገን ከጨረሰ
መሃሉ ዳር ሆኖ፣ ድንበር ከፈረሰ
ህሊና እሺ ካለ የሀገር አበሳ
በደልም ይረሳል ምነው አይረሳ
ህዝብ ከጨረሰ ክፉ ነፍሰ ገዳይ
ሀገርን ከሸጠ ወሮበላ አውደልዳይ
ከተመሳጠረ እጉያው ከገባ
አደራውን ሽሮ ከፈጸመ ደባ
ቢረሳ አይደለም ወይ የወገኑን ስቃይ
ሥልጣንና ሹመት አምሮት ፍቅረ ነዋይ
ይረሳል ይረሳል ኧረ በደንብ አርጎ
ይጥመዋል ለሱ የሰው ደም እንደርጎ
ምን አግብቶት እሱ ሀገር ብትቃጠል
ለማንም ግድ የለው ሆዱ ብቻ አይጉደል
ህሊና እሺ ካለ የሀገር አበሳ
በደልም ይረሳል ምነው አይረሳ
ስብዕናውን ሸጦ ከወላወለ ሰው
እንደመስኖ ውሃ ማንም ከወሰደው
በደልን ይረሳል ጤና የሌለው ሰው
ትልቅ ትንሽ ሆኖ ለራሱ ከሳሳ
በደልም ይረሳል ምነው አይረሳ
ሥልጣንና ሹመት የተመኘ ገንዘብ
የወገኑን ስቃይ አይችልም ለማሰብ
አዲስ አይሁንብህ ይሄ ወለላዬ
ከበፊትም አለ ድጋሚ አሁን ታዬ
ህሊና እሺ ካለ የሀገርን አበሳ
በደልም ይረሳል ምነው አይረሳ
ዋቻሞ
(“በደል ይረሳል ወይ?” ለሚለው የወለላዬ ግጥም የተሰጠ ምላሽ። “በደል ይረሳል ወይ?” የሚለውን ግጥም ለማንበብ እዚህ ይጫኑ!)



