ዱላ ቅብብል (በአቤል ካሳሁንና በማህሙድ ኢድሪስ)
ድንቅ ያፍሪካ አትሌቶች የሚሰሩት ስራ
መላውን ጥቁር ህዝብ እጅግ ስላኮራ፤
መላውን ጥቁር ህዝብ እጅግ ስላኮራ፤
በየደረሱበት በየውድድሩ፣
ታሪክ እየሰሩ፣ ድል እያበሰሩ፤
የናት ምድራቸውን ስም ስላስከበሩ
ለታላቅ ሽልማት
ወደ አፍሪካ አዳራሽ በክብር ተጠሩ።
ከዚያም ጋዜጠኛ- ተናግሮ አናጋሪ የወሬ ሱሰኛ፤
ወደ አንዱ አትሌት ቀርቦ
አድናቆቱን ደልጾ ድምጹን አለዝቦ፤
‘ጽናት በሚጠይቅ በረዥም ርቀት
ታሸንፋላችሁ ሁሌም ያለጭንቀት፣
አምስት ሽ አስር ሺው ውጤቱ ቢያረካም
ዱላ ቅብብሉስ ለምን አይሳካም?’
በማለት ጠየቀ።
ታዋቂው አትሌትም በስሱ እየሳቀ
‘ቀን ከሌት በመስራት ጥረታችን ሰምሮ፣
ውጤታችን አምሮ
በስካሁን ድላችን
ረክቷል ህዝባችን
ዌል.. እንግዲህ ደግሞ ዱላ ቅብብሉን- ለመሪዎቻችን’
ብሎ ተናገረ
በዚህ ንግግሩም ሪከርድ ሰበረ።
አቤል ካሳሁንና ማህሙድ እንድሪስ ካሳተሙት
‘ከ… እስከ’ የግጥም መድብል የተወሰደ



