“የመያድ” ረቂቅ ዐዋጅ የሞት ቅጣት ነው ተባለ
መያዶች ለፍትህ ሚኒስቴር አቤቱታ አቀርበዋል
Ethiopia Zare (ዓርብ ግንቦት 8 ቀን 2000 ዓ.ም. May 16, 2008)፦ መንግሥታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች (መያዶች) “የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት ረቂቅ ዐዋጅ” በሚል የቀረበው ረቂቅ በመያዶች ላይ የተሰነዘረ የሞት ቅጣት ነው በሚል በባለድርሻዎቹ ተተቸ። ረቂቁ ለፓርላማ ከመመራቱ በፊት፣ ሰፊ ውይይት ሊደረግበት እንደሚገባም በመግለጽ ለፍትህ ሚኒስቴር አቤቱታ አቅርቧል ሲል ‘እንቢልታ’ የተሰኘው በሀገር ውስጥ የሚታተም ጋዜጣ በዛሬው ዕትሙ ዘገበ።
ዓርብ ሚያዝያ 28 ቀን 2000 ዓ.ም.፣ 300 የሚጠጉ መያዶች በፍትህ ሚኒስቴር የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተገኝተው በረቂቁ ላይ ውይይት ያደረጉ ሲሆን፣ ረቂቁን ለማየት በቂ ጊዜ ስላልነበራቸው፣ ከመደናገጥ ባለፈ ጠንካራ ተሳትፎ አለማድረጋቸው ታውቋል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ወደ 3 ሺ 500 የሚሆኑ መያዶች ሲኖሩ አብዛኛዎቹ ያሏቸውን ኔት ዎርኮች ሰብስበው ሲወያዩበት መሰንበታቸው ታውቋል።
በመጨረሻም ባለፈው ማክሰኞ ሁሉም በአንድ ላይ ተሰባስበው፣ የአቋም መግለጫ ያወጡ ሲሆን በስብሰባው ላይ ረቂቅ ዐዋጁ በመያዶች ላይ የተሰነዘረ የሞት ቅጣት ነው ብለውታል።
በሁሉም ውይይቶች የተሰነዘሩት ሃሳቦች ተሰብስበውና መያዶችን አያሠራም የተባሉት ነጥቦች ከረቂቅ ዐዋጁ ላይ ተለቅመው ለፍትህ ሚኒስቴር ቀርበዋል።
መያዶችን አያሠራም በሚል ከተነሱት ነጥቦች መካከል የውጭ ማኅበራት በሰብዓዊ መብት፣ በመልካም አስተዳደር፣ በግጭት መፍታት፣ በኮሚኒቲ ዴቨሎፕመንት እንዳይሠሩ የሚከለክል መሆኑ፤ ሕጉ ከሲንጋፖር ሕጋ የተቀዳ መሆኑና፤ ሕጉ የወጣው አገሪቷ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት በምትገዛበት ጊዜ “ቻይኒዝ ሴክሪት ሶሳይቲ” የተባለ እንደ “ሲንጋፖር ነፃ አውጪ” ዓይነት የወንጀለኛ ድርጅት፣ ለመቆጣጠር የወጡ ጨቋኝ ሕግ መሆኑን፤ የኃይማኖት ድርጅቶች ራሱን የቻለ ሕግ ሊወጣላቸው እንደሚገባ፣ ቅጣቶች በጣም የከበዱና የበዙ መሆናቸው በመንግሥት ሹመት የሚቋቋመው ኤጀንሲ ሥልጣን በጣም የሰፋ መሆኑን፣ ፖሊሲ ሳይኖር ዐዋጅ መቅደሙ፣ የውጭ ማኅበራት የኤጄንሲውን ውሳኔ ተቃውመው ይግባኝ ማለት እንዳይችሉ መከልከሉ፤ አያሠሩም ከተባሉ አንቀጾች ጥቂቶቹ ናቸው።
ማኅበራቱ በጋራ ተሰባስበውና ባላቸው ግብረ ኃይል አማካይነት አያሠራም ያሏቸውን ነጥቦች በዝርዝር አስፍረው ለፍትህ ሚኒስቴር እንዳቀረቡና “እንጠራችኋለን” የሚል ቀጠሮ እንደተሰጣቸው ታውቋል።



