“ጊዜ ዱሮ ቀረ!” (ዳግማዊ ዳዊት)
“ጊዜ ዱሮ ቀረ!”
ዳግማዊ ዳዊት
ሰው ተስፋው ሲቀጭጭ - ነገ ሲያስጨንቀው
ዛሬ መከራውን - ግፉን ሲያስቆጥረው
“ጊዜ ትናንት ቀረ! ጊዜ ዱሮ ቀረ!“ - ይሆናል ምስጋናው።
ጊዜ ተስፋ ዳምኖ - የሚዘንብ ሲመስል
ሰው ዛሬ እየከፋው - ይታያል ፈገግ ሲል።
ታዲያ ማነው እርሱ - ተስፋን የሚዘራ
በዛሬ የሚተኩስ - የሰው ባላጋራ
ምድር ነው ወይስ ሰው - የተስፋ ጠላቱ
ሰው ነው ወይ እርጉሙ - ወይንስ ምድሪቱ?
እምቅ ሀብት ሳይኖራት - ጃፓን ስትበለጥግ
ቻይና እልፍ ህዝቦቿን - አልብሳና አጉርሳ - በፍጥነት ስታድግ
አሜሪካ ኃያል ስትሆን- በአራት ዘመን
የሐበሻ ምድር በችግር ሲታመስ - ሲተላለቅ ወገን
ሀገርም ቢኖረው - መንግሥትም ቢኖረው - ሦስት ሽ ዘመን
ማሞገስ መኮነን - ሰውን ወይስ ጊዜን - ወይንስ ምድሪቱን?
ሐበሻ ሐገር ኖሮት - በታሪክ ላይ ሲጣፍ
አውሮጳ ያን ጊዜ - አልወረደም ከዛፍ
ካሌብ ምድረ-ዐረብን - አፍሪካን ሲያስገብር
የአሜሪካ ምድር - አልተቀኘም ነበር
ጉድም እንደ ጅራት - ከኋላ ነውና
ሐበሻ ሲዋረድ - እያየን ነው ገና።
እናም “ዱሮ ቀረ!” የሚባለው ጊዜ
ነውረኛ ንግግር - ሲገፋም አባዜ
አካፋን አካፋ - የምንል ከሆነ
ሰው ነው እንጅ ክፉ - ጊዜ ምን በደለ?
ትናንት ከሚባለው ትናንት ጀምሮ
ምነው አላቆመም - የሐበሻ ሮሮ
ሲያሳድደው ያለው - ከቦረና አስመራ
ከሃርጌሳ አንስቶ - ሴቲቱ-ሁመራ
ለህዝቡ ጦርነት - ሆኖበታል ሥራ።
ጊዜም እንደወተት - ሲገፋ ሲገፋ
ከትናንት የሚሻል - ዛሬ እሚባል ጠፋ።
ሰው ተስፋው ሲቀጭጭ - ነገ ሲያስጨንቀው
ዛሬ መከራውን - ግፉን ሲያስቆጥረው
“ጊዜ ትናንት ቀረ! ጊዜ ዱሮ ቀረ!“ - ይሆናል ምስጋናው።
ዳግማዊ ዳዊት
መስከረም 2003 ዓ.ም.
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.



