ሣህሌ ደጋጎ (ክንፈ ሚካኤል)
ሣህሌ ደጋጎ
ክንፈ ሚካኤል
ዋ ሣህሌ ታላቁ
ጎምቱ የሙዚቃ ሊቁ
አንተም ጨከንክ እንደ ጓገኛህ
በሕይወት እንደ ነበርከው በእልፊትም ተጎዳኘህ።
ተከተልከው ጥላሁንን
አንድ ላይ ነበርክ ምንም ቢሆን።
ክዘ ሲጀምር ዘመናዊ
አንተ ነበርክ መርአዊ።
መሣሪያውን አቀናብረህ
ሳክሱን ከዋሽንት ደምረህ
በፒያኖ በከበሮ አጅበህ
በክላሪኔት በትራምፔት
በክሽ ክሽ በአኮርዲዮን
በአልቶ ሳክስ በአርጋኖን።
ይህን ሁላ መሣሪያ
አደላድለህ ለባለሙያ
አሳለፍክ ስንት አሥርታት
ያገር መኩሪያ ያገር ኩራት።
በሙዚቃ ቅንብር በዜማ ቅላጼ ፈጠራ
ዕድሜህን ሙሉ ስትባክን ለአንዲቱ ባንዲራ
ምንጭ ነበርክ ለብዙ የማትነጥፍ የማታባራ
ዛሬ አሸለብክ አሉኝ ምን አባቴን ገባኝ ግራ።
ሀገሬ ስንቱን አጣች ብዙ ያላት ይመስል
መቼ ይሆን ያሁኑ ካለፈው የሚቀጥል
በል እንግዲህ ሣህሌ ልሰናበትህ ከሩቁ
የመሣሪያውን ስልት የምታውቀው ሊቁ ረቂቁ።
ክንፈ ሚካኤል
መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፪ ዓ.ም.



