ወለላዬ ከስዊድን This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

መቼም ተስፋዬ ገብረአብ ከጻፈ አንድ ትዝታ የሚጭር ወይም ስሜት የሚነካ ነገር አያጣም። ባለፈው ሣምንት ”አሳዛኝ ዜና” በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፉ ደግሞ ስሜቴን መንካት ሳይሆን በክፉ የኀዘን ትዝታ ውስጥ ዘፍቆኝ ሰነበትኩ። እንዴት ሆኖ ማለትዎ አይቀርም፤ እነሆ!

 

 

ንፋስልክ ስብስቴ ነጋሲ የሚባል ትምህርት ቤት አለ። ከአንደኛ እስከ ስምንተኛ ክፍል ትምህርት ይሰጥበታል። ትምህርት ቤቱ በሁለት የተከፈለ ነው። በዮሴፍ ቤተክርስቲያን በኩል ያለው ከአንደኛ እስከ አምስተኛ መማሪያ ነው። ካታንጋ ይባላል። ከፊት ለፊቱ ደግሞ ያለው ከስድስተኛ እስከ ስምንተኛ ክፍል ትምህርት የሚስጥበት ሲሆን፣ ጥላ ፎቅ ይባላል። ማን ካታንጋ እና ጥላ ፎቅ የሚሉትን ቅጽል ስሞች ማን እንዳወጣው እንዳትጠይቁኝ።

 

ከትምህርት ቤቱ አስተማሪዎች መካከል ’ቆዳ’ እያሉ የሚሳደቡት ቲቸር ሀጎስ፣ ትምህርት ቤት ተዘክቶ ሲከፈት አንደኛው ዓይኑ ጠፍቶ ጥቁር መነጽር አድርጎ የመጣው ጋሽ አይናለም፣ ቲቸር መንግስቴ (ጀርጀራው) በቅንፍ ውስጥ ያለው ስም ሁሉም ቦታ ስለሚገኝ የወጣለት ይመስለኛል፣ እማሆይ የግብረገብ አስተማሪዋ። ሳሙኤል አቤ (ፍየሉ) አሁንም ቅንፉ ውስጥ ያለው ቅጽል ስም አገጩ ላይ በተንጠለጠለው ጢሙ የወጣለት ነው፤ ምሳሌ በሰጠ ቁጥር ከንባታን ሳያነሳት አያልፍም። ”መልኩን አሳምሮ እንደወሎ ፈረስ፣ ንግግር አያውቅም እስከዛሬ ድረስ” የምትል የሚደጋግማት ግጥምም ነበረችው። እነዚህ ሊረሱ የሚችሉ አስተማሪዎች አልነበሩም። ሌላ ቀን ስለነሱ እና ስለክፍል ጓደኞቼ የምልዎ አለኝ። ለዛሬ መስመሬን እንዳልስት ወደዋና ነገሬ ልግባ።

 

ወደ ስድስተኛ ክፍል እንዳለፍኩ አንድ የክፍል ኃላፊ መምህር ገጠመኝ። ደልደል ካለ ሰውነት ጋር ጠቆር ያለ መልክና ቡና ዓይነት ዓይኖች ነበሩት። ፊቱ እንደሰውነቱ ሁሉ የሞላ ነው ጢሙ በጥንቃቄ ተላጭቶ አያውቅም። ሁልጊዜ ቀምቀሞ ነው፤ ሲስቅ ደስ ይላል። ብዙ ጊዜ ሲስቅ ግን አይታይም። አለባበሱ ሽቅርቅር ነው ለማለት አያስደፍርም፤ ከሁሉም አስተማሪዎች ጎስቆል ብሎ የሚታይ እሱ ነው። ሆኖም መኪና ያለው ደግሞ እሱ ብቻ ነበር። ሲትሮይን 1131 አ.አ. ታሪካዊ መኪና ስለሆነች እስከታርጋዋ አትረሳኝም።

 

ስለመኪናዋ ትንሽ ላውራ መልኳ በፊት ቤዥ ወይም ነጭ ሳትሆን አትቀርም፤ በኋላ ግን ይሄ ነው መልኳ ለማለት የምታስቸግር አይነት ነበረች። ከፊት ለፊቷ አንድ የዝናብ መጥረጊያ የላትም አንዱም ተሰብሮ ከመስታወቱ ጥግ በኩል የደረቀ ቁስል መስሎ ተለጥፏል። ታጥባ የምታውቅ መሆንዋን እንጃ፤ እስከመስታወቷ በአቧራ የተሽፈነች ናት። ከኋላዋ ያለው አንዱ መብራት መስታወት የለውም አንዱ በፕላስተር ተያይዞ የተንጠለጠለ ነው። የጋቢናው መግቢያ በር በደንበኛው የቤት በር ቁልፍ የተቆለፈ ነው። ጭስ ማውጫዋ ተሰብሮ ሌላ ብረት ተቀጥሎበት ተሳዳቢ ሕጻን ልጅ አስመስሏታል።

 

ቲቸሩ ስንለቀቅ መኪናውን ያስነሳል። በተገኘው ተማሪ ተገፍታ ቶሎ ከተነሳች የቃሊቲን መስመር ይዛ ጥቁር ጭሷን አስፓልቱ ላይ እየነሰነሰች ትጓዛለች። አንዳንድ ቀን ግን አትነሳም። እዛው ስትንተፋተፍ ትቆይና በተማሪ መገፋት ትጀምራለች። አስተማሪያችን መሪውን እያስተካከለ ጉዞውን ይጀምራል። ቃሊቲ እንደሚኖር ስለምናውቅ ከወዲሁ የምንቀረው መንገድ ድረስ ገፍተን ለተረኞች እንተዋለን። ሌሎቹም ለሌሎች ተማሪዎች እያስተላለፏት እስከምትነሳ ድረስ ይዘልቃሉ።

 

ቃሊቲ የዶሮ እርባታ እንደነበረው እንሰማለን። ማንም ተማሪ እርባታውን አየሁ የሚል ባይኖርም እንቁላል ይዞ መጥቶ ጠብሶ እንደሚበላ ግን ብዙዎቻችን እናውቃለን። እኔ ማወቅ ብቻ ሳይሆን አንድ እሁድ ቀን እንቁላል ጥብሴን ከአስተማሪያችን ጋር ገሽልጫለሁ። ይሄንን አጋጣሚ ጽሁፌ ካልተንዛዛ በኋላ አወጋችኋለሁ።

 

ይህ አስተማሪ የክፍል ኃላፊዬ ነው ብያችኋለሁ፤ ጆግራፊ ነበር የሚአስተምረን። አንድ አስተማሪ ወይ ይወደዳል ወይ ይጠላል። እሱን ግን እናከብረውም፣ እንወደውም፣ እንፈራውም ነበር። የተማሪ ስም አይጠራም፣ ማን ቀረ ማን መጣ የለም። ማስተማር በሚጀምርበት ጊዜ ግን አንዲት ኮሽታ አይፈልግም። አርፍዶ መግባትም የለም። ”ስማ የምትማር ከሆነ ተማር፤ የማትማር ከሆነ ውጣ …” ብሎ ያስጠነቀቀው ተማሪ ሳት ብሎት ሲናገር ከሰማው ማስመሪያ ሲፈልግ አይውልም ያን ያንበሳ መዳፍ የመሰለ እጁን አናቱ ላይ ያሳርፍበታል። ጉዳት የሚያስከትለው እጁ አልነበረም፤ ወደአናት ቀድሞ የሚደርሰው ፈርጣም ቀለበቱ ነበር።

 

ፈተና ፈትኖ አርሞ የሚሰጠው ቆይቶ ነው። ለምን እንደሚዘገይ አይገባኝም። ጥያቄዎቹ ከአምስት ወይንም ከአስር አይዘሉም። ለዋናው ፈተናም ከዚህ በላይ ጥያቄ የለም። እያንዳንዳቸው ግን ከአስራ አምስት ወይም ከአስር ነበር የሚታረሙት። አንድ ጊዜ በዓመቱ መጨረሻ የምስክር ወረቀት ሲሰጠን ደረጃውን የሞላው ከአንድ እስከ ሦስት ለወጡት ብቻ ሆኖ ተገኘ። ሌሎቻችንስ ብለን ጠየቅን፤ ”እናንተው ሙሉት” የሚል መልስ ሰጠን። አብዛኞቻችን አንደኛ ወይም ሁለተኛና ሦስተኛ ብለን ሞልተን፤ እኛም ተደስተን ወላጆቻችንንም አስደሰትን። ለነገሩ ጥሩ አድርጎ ስለሚያስተምረን በሱ ትምህርት ሁላችንም ጥሩ ውጤት ነበረን።

 

ይቺ አሰራሩ በአስተዳደሩ አልተወደደችለትም። ትምህርት ቤቱ ሲከፈት የእርሻ አስተማሪ ሆኖ ጠበቀን። ሥራው የተስማማው መስሎ ቢታይም በኋላ በኋላ አንዳንድ ወሬዎች መሰማት ጀመሩ። ከዳሪክተሩ ተጣልቶ እኮ ነው እዚህ የተመደበው፣ በፊትም እኮ ከአየር ኃይል ተጣልቶ ነው እንጂ የወጣው እስካሁን እኮ ፓይለት ይሆን ነበር፣ … እሱማ ፓይለት ሆኗል አይሮፕላኑን ይዞት ይጠፋል ተብሎ ነው፣ … የማይወራ የለም እውነት ለመሆኑ እርግጠኛ አይደለሁም ልናገረው የምችለው ቢኖር በስፖርት የዳበረ ሰውነቱንና የአየር ኃይል አርማ ያለበት ትልቅ ቀለበቱን ነው።

 

የእርሻ አስተማሪ ከሆነ በኋላ አንድ እሁድ ቀን ጠዋት ሽንኩርቴን ውሃ ላጠጣ ወደ ትምህርት ቤት ሄድኩ። መምህራችን የሸሚዙን እጅጌ ስብስቦ በሰፊው የያዘውን የአትክልት ቦታ ይኮተኩታል። ሲያየኝ ሥራውን አቁሞ ወደኔ መጣ። ከጨበጠኝ በኋላ ”ምን ልትሰሪ መጣሽ?” ብሎ ጠየቀኝ ፈገግታው ደስ ይላል።

 

”እርሻዬን ውሃ ላጠጣ”

 

”እንዴ ባዶ እጅሽን? ... በምንሽ ነው የምታጠጪው?” አንዳንዴ ሲልከኝ አንቺ ስለሚለኝ አዲስ አልሆነብኝም።

 

ስቄ ዝም አልኩ። በኋላ ግን እርሻዬን ለማየት ባልኩት ኖሮ ብዬ ተቆጨሁ። ትከሻዬን አቅፎ የትምህርት ቤቱ ደረጃ ላይ ቁጭ አልን። ጠይም ፊቱ ይበልጥ ጠቁሯል። ጫማውና ልብሱ በጭቃ ተለዋውሷል። ትኩስ ትኩስ አፈር ይሸታል። ከንፈሩ ኩበት መስሎ ደርቋል። ፀጉሩ አልተበጠረም። ጺሙ ጎፍሯል … አስተማሪዬ አሳዘነኝ። የማደርግለትን አላውቅም እንጂ አንድ ነገር ባደርግለት ደስ ባለኝ ነበር። እፊት ለፊቱ ባለው እርሻ ላይ አፍጦ ቆየ። በዛው ሁኔታ ለብዙ ደቂቃዎች ቆየ። ካስተማሪ ጋር ምን እንደሚወራ ስለማላውቅ፣ እኔም ዝም ብዬ እሱ በሚያየው አቅጣጫ አፈጠጥኩ።

 

ከብዙ ቅይታ በኋላ ”ቲቸር” ብዬ ተጣራሁ።

 

ዞር ቦሎ አየኝ። ”ውሃ ላጠጣ?”

 

”አዎን!” የሱን ውሃ ማጠጫ አመላከተኝ።

 

እርሻዬ ወጣ ወጣ ባሉ አረንጓዴ የሽንኩት ቅጠሎች ተሸፍኗል። እጉን እጎኑ ያለውን ባዕድ ቅጠል እየነቀልኩ ደህና አድርጌ ውሃ አጠጣሁት። ማጠጫው ተስማምቶኛል፤ ባለወንፊት አፍ አለው። ውሃው ብትን ብሎ ስለሚፈስ ደስ ይላል። እርሻዬ እንደዛን ቀን ውሃ ጠጥቶ አያውቅም። ወደአስተማሪዬ ስመለስ መጥበሻና እንቁላል አዘጋጅቷል። መጥበሻውን ሦስት ድንጋዮች ላይ አስቀሞታል። ከስሩ እንጨት አለ። ወደ እርሻው ቦታ ሄዶ እርጥብ ሽንኩርትና የደረሱ ቃሪያዎች ይዞ ተመለሰ።

 

”ጨረሽ?”

 

”አዎን!”

 

”በይ ሂጂና ዳቦ ገዝተሽ ነይ” ብሎ ስሙኒ ሰጠኝ። በአምስት ሣንቲም ሁለት ሂሳብ፣ አስር ጥምዝ ዳቦ ይዤ ከች አልኩ። እሳቱን አንድዶ እንቁላሉን እየጠበሰ ነው። እንቁላል የመታበት ዕቃና ታጣፊ ጩቤ እጎኑ ተቀምጠዋል። አንድ ትሪም ታጥቦ ድንጋይ ተደግፎ ቆሟል። ባንዲራ የያዘ አንበሳ ስዕል ማህሉ ላይ አለበት። መኪናዋ እንደ ዕቃ ቤትም እንደምታገለግል ገባኝ።

 

ሁለት ለስላሳ እንድገዛ እንደገና ላከኝ። አንድ ብሩን አስዤ ሁለት ትልልቁን ጠርሙስ ኮካኮላ ይዤ መጣሁ። አሁን እንቁላሉ ደርሷል፣ በትሪው ላይ ተዘርግፎ ዙርያውን ዳቦ ከቦታል። ሽታው አካባቢውን አውዶታል።

 

እንቁላላችንን ጥርግ አድርገን በላን። እስከዛሬ ድረስ እንደዛን ቀን እንቁላል ጥሞኝ አያውቅም። በመሃል በመሃል አንዳንድ ጥያቄዎች ይጠይቀኝ ነበር። እኔም ስፈራ ስቸር አንድ ጥያቄ አቀረብሁ። ”ለምን ወደ እርሻ አስተማሪነት ተቀየርክ?” አልኩት። ከት ብሎ ሳቀ። ወድያው ደግሞ ግንባሩን ቅጭም አድርጎ አዘነ። ብዙ ግን አልቆየም ”ገበሬ ስለምመስል ነው” አለኝ። አከታትሎ ”አልመስልም እንዴ?” ብሎ ጠየቀኝ። ምን እንደምመልስ አልገባኝም፤ ዝም አልኩት። ካስተማሪዬ ጋር በእንዲህ አይነት ሁኔታ ያሳለፍኳትን ቀን ዕድሜ ልኬን አልረሳትም።

 

በሚቀጥለው ዓመት አስተማሪዬን እዛው ጥዬው ወደ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ተዛወርኩ። አሁን እናስ? ማለትዎ አይቀርም፤ ይህ መምህሬ በላይነህ ገብረማሪያም ይባላል። በመግቢያዬ እንደጠቀስኩት ተስፋዬ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ በሆነኝ ጽሁፉ ያነሳው መምህሬ የነበረው መምህር በላይነህ ገብረማሪያምን ነው። ተስፋዬ በስንት ጊዜው አንስቶብኝ ለመምህሬ አንጀቴ ተላወሰ። እንባ እንባ እንዳለኝ ዋልኩ፣ ሰነበትሁ።

 

ከስልሳ ስድስቱ አብዮት በኋላ ጋሽ በላይነህ እዛው ቃሊቲ እንደሚኖር አውቅ ነበር። በስልሳ ሰባት መጨረሻ ወይም በስልሳ ስምንት መካከል ላይ ይመስለኛል የጥናት ክበብ እየተባለ ወጣቶች በየቀበሌው እንሰበሰብ ነበር። ፍቅር እስከመቃብርን እናነባለን። ስለሱ ትንተና የሚሰጡ ልጆች አሉ። በዛ ስብስብ በስተጀርባ ኢህአፓ ስሯን እየዘረጋች ነበር። አንድ ቀን እዛው ጥናት ክበብ እንደተሰበሰብን ጋሽ በላይነህ መጣ። ከድሮው በይበልጥ ተጎሳቁሏል። ወፍራም ፈገግታው አሁንም አለ። ሽንትር ሽንትር ያለው ወፍራም ሹራብ ለብሷል። ሰላምታ ሰጥቶን በአንዳንድ ሁኔታዎች ላይ ንግግር አደረግልን። የተወሰኑ ልጆችም ጋር በግል ተነጋግሮ ሄደ። እንደመሰለኝ ኢህአፓን እየዘረጋና መልዕክት እያስተላለፈ ነበር። ... ቆይቼ በኢህአፓ ውስጥ ትልቅ ሥፍራ እንዳለው ተረዳሁ።

 

ከዛ በኋላ የአብዮቱ ማዕበል ሀገሩን ያምሰው ጀመር። ጋሽ በላይነህን ከዛች ቀን በኋላ አይቼው አላውቅም። ቆይቶ በእንደሞተ ሰማሁ። ምን እሱ ብቻ ወጣት እንደቅጠል ረገፈ። አብዮት እንኳን ተቀናቃኟን፤ የገዛ ልጆቿን ጭምር በላች። ያ ሁሉ አለፈና ወያኔ ሀገሪቷን በተቆጣጠረ ማግስት ተስፋዬ ስለጋሼ በላይነህ ”በእፎይታ መጽሔት” ጽፎ አነበብኩ። መርዶውን በወጉ አረዳኝ ስቅስቅ ብዬ አለቀስኩ። ዛሬ ደግሞ ”አሳዛኝ ዜና” በሚለው ጽሁፉ አንስቶት የተቀበረ ኀዘኔን ቀሰቀሰብኝ። አስተማሪዬ ለተነሳበት ዓላማ በቆራጥነት ታገለ። ሊቀመንበር መንግሥቱን ሳይቀር መግቢያ መውጫ አሳጥቶ፣ ቤተ መንግሥት እንዲመሽጉ አደረገ። በመጨረሻም ከስቃይ ሁሉ የከፋ ስቃይ ደርሶበት በጀግንነት ሞተ። እነሆ ይሄ ከሆነ ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ አለፉ። አራተኛው ሊገባደድም ሁለት ዓመታት ቀሩት።

 

አፈሩን ያቅልለትና … ”ልጆች በርትታችሁ ተማሩ! ለዚች ለወደቀችና ለተጎሳቆለች ሀገር ተስፋዋ እናንተ ናችሁ!” … ይለን ነበር። ድምፁ እስከዛሬ ድረስ ጆሮዬ ላይ ይጮሃል።

 

አይ! ጋሽ በላይነህ እህ! …


ወለላዬ ከስዊድን This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ