ለቅሶ እንድረስ (አበራ ለማ)
አበራ ለማ
(ግጥሙን በፒ.ዲ.ኤፍ. ለማንበብ እዚህ ይጫኑ!)
ቀብር ውጡ ወዳጆቼ - ጌታ ብዕር አረፈ
ደራሲው ሰው ሆነ - ፈጣሪነቱን ተገፈፈ፤
በመጋኛ ተቦትልኮ - በዘር ሀረግ ተጠርንፎ
ጌታ ብዕር ተሻረ - ካባ ማዕረጉን ተገፎ
የት ይደርሳል ያልነው ጎበዝ - ተስፋ ያልነው ሽል ጨንግፎ፤
ቀብር ውጡ ወዳጆቼ - ልባችሁ ባዘን የቆሰለ
ፈጣሪው ሰው ሁኖ - ብጤ ፈጣሪን ከሰለለ፤
የብዕር አምላክ ቢቆጣ - በየቤቱ ቢገነፍል
ዘር ማንዘር ብሎ ነገር - የብዕር ጌታን ሲገድል
ማን ይችላል ወዳጆቼ - ማን ይዳኛል ይህን በደል?
ቀብር ውጡ ወዳጆቼ - እግዚኦ ብቻ ነው 'ሚበጀው
ለካስ ብዕርም ይሞታል - ፈጣሪ አምላኩ ሲበድለው
ደራሲ ፈጣሪነቱን ትቶ - የዘር እርሻ ካረገው፤
ቡዳ ቤት ሰላቢ ገባ - ብዕር ተረታ በሞቱ
ፈጣሪም ሰው ሆነ - ሰው ለሥጋው በማድላቱ፤
ቀብር ውጡ ወዳጆቼ - የብዕር ሞት የቆጫቸሁ
የቦለቲካ ሾተላይ - ስልጡን ብዕሩን የነሳችሁ፤
የብሩህ ቀለሙ ጌታ - የጥበብ እስትንፋሱ መገኛ
ወጣቱ መልከ ጸዴቅ - ወዳጄ ልቤው ብዕረኛ፤
ነገሩ ሁሉ ከሆነ - ጌታም ለሥጋው አደላ
ሰውነቱን ማወቅ እንጂ - ፈጣሪነቱማ ተከላ፤
የጥሁፋችን መጣምር - የጥበብ ጌጡ ተስፋ
እንዲህ ተመንገድ ቀርቶ - ተጃችን ላይ ታንቀላፋ፤
ለቅሶ እንድረስ ጎበዝ - ዓለም ሲያሳየን ገመና
የብዕር ሞትን እያየን - ለማንም አይበጅ ጽሞና፤
አዎን! ... ፈጣሪው ሰው ሆነ - ለሥጋ ሥጋው እያደላ
ብዕር ሥጋ ሆነ - ሰው ሥጋውን እየበላ፤
የዘር ቦለቲካን እንርገም - የተስፋን ብዕር ለማዳን
ከዘር ጥላቻ እንመንጥቀው - ይድን ይሆናልና አንድ ቀን፤
ቀብር እንውጣ ወዳጆቼ - ለብዕር ሞት እናልቅሰው
ጥላቻን እንጥላው -
ደረት መተን፣ ሙሾ ሞሸን እንቅበረው!
አበራ ለማ
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.



