አመሰግናለሁ! (በፈቃዱ ሞረዳ)
በፈቃዱ ሞረዳ
የ'ድራችሁ ጣት ቅሳሮ
በዘር ጥቅሻ አሻግሮ
ቢሸነቁጠኝ አባሮ
ሰደደኝ ለዘር ቁፋሮ።
ስንቅ የሚሆን ዘር ቋጥሬ
የዘር አደና ጀምሬ
ዘረኝነትን አየሁት
ወጉን ከ'ናንት ተምሬ።
እንጂ እኔማ አስተዳደጌ
ሰውኛ ክህነት ተክኜ
የተፈጥሮን ኦሪት ሞቲ
የቃሉን ፍቅር ታጥኜ።
ዘሬን ባላሸተው ኖሮ
ተውሼ ከእናንት አፍንጫ
ባልወረድኩኝ በመሰስታ
ለቅርምቻ የዘር ቅርጫ።
ብጠመቀው ነው በ'ናንተ
ብቀምሰው ቅብዓቅዱሱን
ብቀራ ነው ከዳዊቱ
የጎሣን ሥር ሥር መማሱን።
እንጂ የነፍሴማ እውነት
ያውላላው ዓለም ምስጢሯ
እንደዘሬ አስተምርሆ
ዘረሰው ነበረ ዘሯ።
ዘሬን ባላሸተው ኖሮ
በእናንተው ግድ ባይነት
እስከመቼውም አላውቀው
የእናንተንም ዘረኝነት።
ዘር - እኝኝነት።
... ኝኝነት።
በፈቃዱ ሞረዳ
ዘረኝነትን ለሚያወግዙ ዘረኞቻችን (ዘረእኛዎቻችን)



