ዝምታህ ጮኸብኝ (ዳግማዊ ዳዊት)
ዝምታህ ጮኸብኝ
ዳግማዊ ዳዊት
አንተ ፀጥ ያልከው ሰው - አንት የተሎጎምከው
አጥርህ ዙሪያ ታጥሮ - በርክን የዘጋኸው
ሰው መሃል ሆነህ - ከሰው ልጅ የራከው
ለምስጋናም አሜን
ለእርግማንም አሜን
አሜን በፀጥታህ - አሜን አሜን ያልከው
ዝምታህ ጮኸብኝ - ጆሮየውን በጠሰው
እባክህ ተናገር - ዝምታህም ያብቃ
ዝምታ ትብብር - ከበዳይ አለቃ
መሆኑን እወቀው - የዝምታ ደሞዝ
ዝምታ ጠላት ነው - ይኸን እወቅ ጎበዝ።
ነጎድጓድ ባልሰማም - የመብረቅ ብልጭታ
የአውሎ ነፋስ ጩኸት - የዝናብ እሩምታ
መርዶን- ተከትሎ - ደረት ባይመታ
“ወየው ወይኔ!” ባይኖር እንባም መንታ መንታ
ዝምታ ረብሻ ነው - ከጩኸት የበዛ
ህሊናን በጭንቀት - ሰው በአሳር የገዛ።
አወይ ገለልተኛ - አወይ ትርምሱ - አወይ ግሳንግሱ
የዝምታ ጓዙ - በየትኛው ድልድይ - ይሻገራል እሱ
ከእኛ እሚባል እኛ - አሻግሮ የሚያይ ጠፍቶ
ልዩነት ይታያል - ከአንድነቱ ጎልቶ
አወይ ገለልተኛ - ምነዋ አንናገር - አንደበት ተዘጋ
ለአገራችን ጉዳይ - ማንስ ለእኛ ያውጋ
ምነው ዝም የምንል - ህዝብ እየተወጋ?
አሜን በፀጥታህ - አሜን አሜን ያልከው
ዝምታህ ጮኸብኝ - ጆሮየውን በጠሰው
እባክህ ተናገር - ዝምታህም ያብቃ
ዝምታ ትብብር - ከበዳይ አለቃ
መሆኑን እወቀው - የዝምታ ደሞዝ
ዝምታ ጠላት ነው - ይኸን እወቅ ጎበዝ።
ዳግማዊ ዳዊት
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ግንቦት 2002 ዓ.ም.



