ብዕር ሆይ! (ለሎሬት ፀጋዬ ከወልደ አማኑኤል)
ብዕር ሆይ!
ከወልደ አማኑኤል
(ለሎሬት ፀጋዬ ገብረመድኅን መታሰቢያ)
ብዕር ሆይ!
ማነው ፀጋሽን የገፈፈሽ
የቀለም ብልቃጡን ማነው ያነጠፈብሽ?
ሕመም ይሆን የሰው ልጆች ጠላት
ስደት ይሆን የሀገር ፍቅር ናፍቆት
የመድረክ ንጉሦች ወጋየሁና አውላቸው
ድረስልን ብለውት ይሆን ቴአትር ትወና ናፍቋቸው
ወይንስ መንግሥቱ ለማ፣ የቅኔ ረሃብ ጠንቶበት
“ፀጋዬ” ብሎ ሲጠራው፣ ጥሪውን ሲያከብርለት
ብዕር ሆይ!
ማነው ፀጋሽን የገፈፈሽ
መልስም የለሽ
ዋይ! ከአሁኑ ዝምታ ዋጠሽ
ዓርማውን የሚያነሳ ተተኪም ልጅ የለሽ
ብዕር ሆይ!
ይብላኝ ላንች እንጅ እኛ ምን ጎድሎብን
የእሾህ አክሊልና በልግ የከርሞ ሰው በእጃችን
እሳት ወይ አበባ፣ ኦቴሎና ሐምሌትን
በንባብ እንጠግባለን ከመደርደሪያችን አውጥተን
ቢሻን በትዝታ - መድረክ ቴአትር እየቃኘን
ሀሁ አቡጊዳ፤ መልዕክተ ፐፑ እንላለን
ብዕር ሆይ!
ጥናቱን ይስጥሽ
ዳግም የማይገኝ ፀጋሽን ነው የተገፈፍሽ
ከወልደ አማኑኤል
(ፀጋዬ ያረፈ ሰሞን የዛሬ አራት ዓመት ገደማ የተደረሰ)



