አንዷ ጋዜጠኛ ክስ ተመስርቶባት በዋስ ስትፈታ፣ ሁለቱ ታስረው አደሩ

Habte Tadesse, journalist, dupty editor-in-cheif of Enbilta weekly Amharic newspaper

ጋዜጠኛ ሀብቴ ታደሰ

Atenafu Alemayehu, journalist, editor of Enbilta weekly Amharic newspaper

ጋዜጠኛ አጥናፉ አለማየሁ

Ethiopia Zare (ኀሙስ ጥቅምት 13 ቀን 2001 ዓ.ም. October 23, 2008)፦ የቴዲ አፍሮን ክስ የሚያስችሉትን ዳኛ የአባት ሥም በስህተት ያተመው የእንቢልታ ጋዜጣ ሦስት አዘጋጆች በዛሬው ዕለት ችሎት ቀርበው አሣታሚና ዋና አዘጋጅዋ ጽዮን ግርማ እስከ ሦስት ዓመት ሊያስቀጣ በሚችል ክስ ተመስርቶባት በዋስ ስትለቀቅ፤ የሁለቱን አዘጋጆች ጉዳይ ዓቃቤ ሕግ ክሴን አላጠናቀቅሁም በማለቱ ታስረው እንዲያድሩ ተደረገ።

”የቴዲ አፍሮን ጉዳይ የሚያስችሉት ዳኛ ከችሎት ተነሱ” በሚል ርዕስ በመስከረም 23 ዕትሙ አዲስ የተተኩት ዳኛ መሐመድ ዑመር ቢሆኑም ጋዜጣው ዳኛ መሐመድ አሚን ሳኒ ናቸው በሚል የዳኛውን የአባት ስም በስህተት በመዘገቡ ሦስት የጋዜጣው አዘጋጆች ከረቡዕ ጀምሮ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን መዘገባችን አይዘነጋም።

 

በዛሬው ዕለት የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ሦስቱም አዘጋጆች ቀርበው የነበረ ሲሆን፣ ዓቃቤ ሕግ በዋና አዘጋጅዋ ጽዮን ግርማ ላይ ብቻ ”የወንጀለኛ ሕግ ቁጥር 431ሀ እና 486ለ”ን በመጥቀስ ክሱን መስርቶባታል። ፍርድ ቤቱ ለጊዜው በሁለት ሺህ ብር ዋስ እንድትፈታና የፊታችን ሰኞ ጥቅምት 18 ቀን 2001 ዓ.ም. እንድትቀርብ አዟል። ጋዜጠኛው ዋስትናዋን አሟልታ ዛሬ ማምሻውን ከእስር መለቀቋን ከአዲስ አበባ የደረሰን መረጃ ይጠቁማል።

 

በጋዜጣው ምክትል አዘጋጅ ሀብቴ ታደሰ እና በአዘጋጁ አጥናፉ አለማየሁ ላይ ግን ክሴን አለጠናቀቅሁም በማለቱ ሁለቱ ጋዜጠኞች በፖሊስ ታጅበውና በካቴና ታስረው በድጋሚ ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ታስረው እንዲያድሩ ተደርጓል።

 

ጋዜጠኞች ሲከሰሱ ጉዳያቸው የሚታየው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 10ኛ ወንጀል ችሎት የነበረ ቢሆንም፣ ዛሬ የጋዜጠኞቹን ጉዳይ ያየው 14ኛ ወንጀል ችሎት ነው። ይህ ችሎት ”ፈጣን ችሎት በመባል የሚጠራ እንደሆነና እጅ ከፍንጅ የተያዙ የስርቆት ወንጀሎች እንደሚታዩበት በትናንትናው ዕለት መዘገባችን አይዘነጋም።

 

በዚህ ችሎት የሚቀርቡ ጉዳዮች ውሳኔ የሚጥባቸው የዕለቱ ዕለት ወይንም ከበዛ በአንድ ሣምንት ጊዜ ውስጥ ነው። ይህንን የጋዜጠኞቹን ክስ በዚህ ችሎት ለምን እንዲታይ ማድረግ እንዳስፈለገ በግልጽ የታወቀ ነገር ባይኖርም፤ ጉዳዩን እየተከታተሉ ባሉ ወገኖች ዘንድ ግን ጥርጣሬን እንዳሳደረ ለመረዳት ችለናል።

 

በዋና አዘጋጅዋ ክስ ላይ በተጠቀሰው አንቀጽ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የወንጀለኛ ሕግ ቁጥር 431ሀ እና 486ለ፤ ”በማናቸውም አይነት ማሳጣት ወይም ሌላ ዘዴ ጥርጣሬን ያስፋፋ፣ ጥላቻን ያነሳሳ ወይም የኃይል ድርጊት ወይም የፖለቲካ የዘር ወይም የኃይማኖት ኹከት የቀሰቀሰ እንደሆነ፤ በቀላል እስራት ወይም በመቀጮ ወይም ወንጀሉ ከባድ በሆነ ጊዜ ከሦስት ዓመት በማይበልጥ ጽኑ እስራት ይቀጣል” እንደሆነ ለማረጋገጥ ችለናል።

 

በዚህም መሠረት ፍርድ ቤቱ አዘጋጅዋን የፊታችን ሰኞ ጥፋተኛ ብሎ ከወሰነባት እስከ ሦስት ዓመት የእስራት ቅጣት ሊቀጣት እንደሚችል ታውቋል።

 

ጉዳዩን እየተከታተሉ ያሉ የኢትዮጵያ ዛሬ ምንጮች በእስር እንዲያድሩ የተደረጉት ጋዜጠኛ ሀብቴ ታደሰ እና ጋዜጠኛ አጥናፉ አለማየሁ በነገው ዕለት ሊፈቱ እንደሚችሉ ያላቸውን ግምት ገልጸዋል።

 

ጋዜጠኛ አጥናፉ አለማየሁ በጦማር እና በጦቢያ ጋዜጦች ላይ በምክትል አዘጋጅነትና በዋና አዘጋጅነት ሠርቷል።

 

ምክትል አዘጋጁ ጋዜጠኛ ሀብቴ ታደሰ ደግሞ በሀገር ውስጥ በሚታተሙ ከስድስት በላይ ጋዜጦች ላይ እስከ አዘጋጅነት ሠርቷል። እንዲሁም ”ኔቸር” የተሰኘ በኢንቫይሮመንት ላይ የሚያተኩር የራሱን ጋዜጣ ያሣትም ነበር።

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ