አትሌት ቲኪ ገላና ክብረወሰን ስታስመዘግብ Tiki Gelana of Ethiopia celebrates as she crosses the finish line to win the gold

Ethiopia Zare (እሁድ ሐምሌ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. August 5, 2012)፦ በለንደኑ ኦሎምፒክ በዛሬው ዕለት በተካሄደው የሴቶች ማራቶን ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ቲኪ ገላና ውድድሩን በ2፡23፡07 ሰዓት አንደኛ ወጥታ በመጨረስ የወርቅ ሜዳሊያ ከማግኘቷም በላይ የኦሎምፒክ ክብረወሰንን ሰብራለች።

 

አትሌት ቲኪ ገላና በለንደኑ ኦሎምፒክ የሴቶች ማራቶን በአሸናፊነት ክብረወሰን ስትሰብር Tiki Gelana of Ethiopia celebrates winning the Marathon

 

በሴቶች ማራቶን የኦሎምፒክ ክብረወሰን 2፡23፡14 ሰዓት የነበረ ሲሆን፣ የተመዘገበውም በ2000 እ.ኤ.አ. በተካሄደው በሲድኒው ኦሎምፒክ በጃፓናዊቷ አትሌት ናዑኮ ታካሃሺ ነበር። ዛሬ አትሌት ቲኪ ገላና ሰዓቱን በሰባት ሰከንድ አሻሽላ የኦሎምፒክን ክብረወሰን ሰብራለች።

 

አትሌት ቲኪ ገላና የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘቷን ካረጋገጠች በኋላ ዕረፍት ስታደርግ Gold medalist Tiki Gelana of Ethiopia rests at the finish line

በዚህ ውድድር የተሳተፉት ሦስት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሲሆኑ፣ አትሌት ማሬ ዲባባ በ2፡28፡48 ሰዓት ውድድሩን በ23ኛነት ጨርሳለች። አትሌት አሰለፈች መርጊያ ደግሞ ውድድሩን በ2፡32፡03 ሰዓት በመጨረስ 42ኛ ወጥታለች።

 

ኬንያዊቷ ፕሪስቻ ጄፕቱ በ2፡23፡12 ሰዓት ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ ስታገኝ፣ ሩሲያዊቷ ታቲያና ፔትሮቫ ደግሞ በ2፡23፡29 ሰዓት ሦስተኛ በመውጣት የነኀስ ሜዳሊያ አግኝታለች። ኬንያዊቷ ማሪያ ጄፕኮሰጌ ኬታኒ ደግሞ በ2፡23፡56 ሰዓት በመግባት ውድድሩን በአራተኝነት ጨርሳለች።

 

ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ቲኪ፣ ኬንያውያኖቹ ፕሪስቻ እና ማሪያ እንዲሁም ሩሲያዊቷ ታቲያና አርባውን ኪሎ ሜትር ሳይለያዩ ሲሮጡ የነበሩ ሲሆን፣ ውድድሩ ሁለት ኪሎ ሜትር ሲቀረው አራተኛ የወጣችው ኬንያዊቷ ማሪያ ትንሽ ወደኋላ ስትቀር ሦስቱ አትሌቶች ሳይለያዩ አንድ ኪሎ ሜትሩን ዘልቀዋል።

 

ኢትዮጵያዊቷ ቲኪ ገላና በመጨረሻው አንድ ኪሎ ሜትር ሲቀር የመሪነቱን ስፍራ ጨብጣ Ethiopia's Tiki Gelana leads to win the Women's Marathon

ውድድሩ አንድ ኪሎ ሜትር ሲቀረው ግን ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ቲኪ ገላና ቀድማቸው በመውጣት የማሸነፍ ብቃቷን ከማሳየቷም በላይ ለኢትዮጵያም እና ለራስዋ የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳሊያ ከማስገኘቷም በተጨማሪ የክብረወሰን ባለቤት ለመሆን በቅታለች።

 

በለንደን ኦሎምፒክ የኢትዮጵያ ደረጃ

በለንደኑ ኦሎምፒክ የሴቶች ማራቶን ከተጠናቀቀ በኋላ ኢትዮጵያ በሁለት የወርቅ እና በአንድ የነኀስ ሜዳሊያዎች በሀገሮች የሜዳሊያ ደረጃ ሠንጠረዥ 19ኛ ላይ ትገኛለች።

 

ኢትዮጵያ በኦሎምፒክ የሴቶች ማራቶን

የመጀመሪያዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት በኦሎምፒክ የማራቶን ሜዳሊያ ያስመዘገበችው ፋጡማ ሮባ ስትሆን፣ እ.ኤ.አ. በ1996 አትላንታ ላይ ተደርጎ በነበረው ኦሎምፒክ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ በማግኘት ነበር። ከዚያ በፊትም ሆነ በኋላ ኢትዮጵያ በሴቶች የኦሎምፒክ ማራቶን ምንም አይነት ሜዳሊያ ያላገኙ ሲሆን፣ አትሌት ቲኪ ገላና ሁለተኛዋና የኦሎምፒክ ክብረወሰን ለመስበር በቅታለች።

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ