በእነአቶ ጃዋር የክስ መዝገብ ምስክሮች መሰማት ጀመሩ
አቶ ጃዋር መሐመድ
አቶ ጃዋር በግል እንዲታከሙ ትእዛዝ ተሰጥቷል
ኢዛ (ሐሙስ ነኀሴ ፲፬ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. August 20, 2020)፦ በእነአቶ ጃዋር መሐመድ መዝገብ ተቋርጦ የነበረው የዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን የመስማት ሒደት ዛሬ ሐሙስ ነኀሴ 14 ቀን 2012 ዓ.ም. ተጀመረ። አቶ ጃዋር በማላውቀው ሐኪም መነካት አልፈልግም አለ።
ከሦስት ቀን በፊት አቶ ጃዋር መሐመድ ታምሜአለሁ ብሎ መሰማት የነበረባቸው ምስክሮች ተቋርጦ የነበረ ሲሆን፤ ዛሬ ግን የዓቃቤ ሕግ ምስክሮች መሰማት የጀመሩ ቢኾንም፤ አቶ ጃዋር ሕመም ላይ ስለኾንኩ በግል ሐኪም ልታከም ብሎ ያቀረበውን ጥያቄ ፍርድ ቤቱ ተቀብሎታል።
በግሉ ሐኪም ካልኾነ በሌላ መታከሙን የማልፈልገው ለሕይወቴ ስለምሠጋ ነው በማለት ጭምር ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል። ዓቃቤ ሕግ በበኩሉ የሕክምና አቅርቦቱ እያለ ወደሌላ የሕክምና መስጫ መውሰድ አግባብ አለመኾኑንና ይህንን ማድረግ ሕገ መንግሥታዊ ያለመኾኑን አስረድቷል።
ሁሉም ሰው እኩል ስለመኾኑ የገለጸው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፤ ወደ ግል ሐኪም መሔድ የሚችሉት ከመንግሥት ሕክምና በላይ የኾነ ሕክምና ሲያስፈልግ ብቻ ነውም በማለት የመከራከሪያ ሐሳብ አቅርቧል። ኾኖም ፍርድ ቤቱ አቶ ጃዋር በግል ሐኪም እንዲታዩ ትእዛዝ ሰጥቷል። (ኢዛ)



