ምርጫ ቦርድ የመራጮች ምዝገባና ቁሳቁሶችን ግዥ አጠናቅቆ አስገባ
ከፍተኛ ጥበቃ ባለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የካርጎ መጋዘን ውስጥ ይገኛሉ
ኢዛ (ሰኞ የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. February 17, 2020)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በምርጫ 2012 የመራጮች ምዝገባና ቁሳቁሶችን ግዥ አጠናቅቆ አስገባ።
ምርጫ ቦርድ እነዚህን ቁሳቁሶች ከፍተኛ ጥበቃ ባለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የካርጎ መጋዘን አስገብቶ ማጠናቀቁንም ገልጿል። በዚሁ መረጃው የቁሳቁስ ድልድል ሥራው በቅርቡ እንደሚጀመር ጠቅሷል።
ቦርዱ ከዚህ ቀደም አስታውቆ እንደነበር ከምርጫ ቁሳቁሶች ውስጥ የምዝገባ ሰነዶች፣ ሕትመትና ቁሳቁሶችን በዱባይ የሕትመት ሥራው እንዲጀመር ስምምነት መፈራረሙ ይታወሳል። ይህንን ትእዛዝ የሠጠውና የተፈራረመው የዛሬ ሁለት ወር ታኅሣሥ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. እንደነበር መዘገባችን አይዘነጋም። (ኢዛ)