ጆን ኬሪና አልባራዴ አሸባሪዎች ናቸውን?
ግርማ ካሳ
ኢቲቪ በቅርቡ አንድ፣ በአንድ በኩል አሳዛኝ፤ በሌላ በኩል አስቂኝ ዶኪሚንተሪ ለተመልካቾቹ አቅርቧል። በርካታ ጉዳዮች ተነስተዋል። በዚህ ጽሑፍ የፌዴራል ከፍተኛ አቃቤ ሕግ የሆኑት፣ አቶ ብርሃኑ ወንድማገኝ፣ አንጋፋው ጋዜጠኛ እስክንደር ነጋን በተመለከተ፣ በተናገሩት ላይ ጥቂት ሃሳቦችን ለመገልጽ እወዳለሁ።
ሰውዬው ስለሕግ፣ ስለሕገ-መንግሥቱ እየደጋገሙ አውርተዋል። ማንም ሕገ-መንግሥቱን የማክበርና የማስከበር ኃላፊነትና ግዴታ እንዳለበት የገለጹት፣ አቃቤ ሕጉ፣ የሀገሪቷ ሕግ ሲናድ ወንጀለኞችን ይዞ ለሕግ ከማቅረብ ወደኋላ እንደማይሉ አሳስበዋል። በርግጥ ወንጀለኛ መያዝና መቀጣት አለበት። ሕግ መከበር አለበት። ይሄ ብዙ አያከራክረንም።
ነገር ግን "ሕግ፣ ሕግ" እየተባለ፣ ፍፁም ሕገ ወጥ የሆነ ተግባራት፣ ሕግ አስከባሪ ነን በሚሉ እየተፈጸመ መሆኑ ነው ብዙ እያከራከረን ያለው። ሕግ ሁላችንንም በእኩልነት የሚዳኝ መሆኑ ቀርቶ፣ ጥቂቶች እንደፈለጉ የሚገለባብጡት፣ የመጨቆኛ መሣሪያ በትር መሆኑ ነው እያሳሰበን ያለው።
አቶ ብርሃኑ፣ ስለእስክንድር ነጋ ሲናገሩ "የእስክንድርንም ኬዝ ቢሆን፣ የ2004 ዐረብ ስፕሪንግ አይነት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የአመጽ ጥሪ በማድረግ ከተንቀሳቀሱ ኃይሎች አንዱ እራሱ ነው። እርሱ በተለይም በየትኛውም አርዕስት ላይ በመጻፉ ምክንያት፣ አንድም ክስ አልቀረበበትም። የእስክንድር ጉዳይ ከፍሪደም ኦፍ ኤክስፕረሽን፣ ከመናገር ነፃነት ጋር፣ ከመናገር መብት ጋር የተያይዘ በፍፁም አይደለም። ቅድም እንዳልኩት፣ የአመጽ ጥሪ ማስተላለፉ ነው። የአምጽ ጥሪው ደግሞ የግንቦት ሰባት ተልዕኮን ለማሳካት ነው። ከዚህ ጋር እስከ ፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ድረስ በጣም ሰፋ ያሉ ክርክሮችን በተደጋጋሚ አድርገናል። የሀገሪቱ የመጨረሻ የሆነው ፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፤ የጥፋተኝነት ውሳኔ ሰጧል።" ነበር ያሉት።
በግብጽ የታየው፣ በኢትዮጵያም እንዲደገም እስክንደር ነጋ የሚፈልግ እንደነበረ የታወቀ ነው። በአንድነት ጽ/ቤት በተደረገ ስብሰባ ላይ "እንችላለን! በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች እንደሚቻል አይተናል። ኢትዮጵያ ከእነሱ ቢያንስ ቢያንስ አታንስም። ታሪክ እንሥራ!" ያለውና ኢቲቪ ቀንጥቦ ያወጣው አባባል ትክክለኛ አባባል ነው። እስክንደር ነጋ፣ ይሄን አልካዳም። ሊክድም አይችልም። እኛም እስክንድር ባለው እንስማማለን።
"እስክንደር፣ በግብጽ የተከሰተው በኢትዮጵያ እንዲከሰት መፈለጉና በዚያ ዙሪያ መንቀሳቀሱ በምን መስፈርትና ሚዛን ነው ሽብርተኝነት ተደርጎ ሊወሰድ የሚችለው?" በሚለው ላይ ነው ሌላው ክርክራችን። በግብጽ የነበረው እንቅስቃሴ፣ ፍጹም ሰላማዊ የነበረ እንቅስቃሴ ነው። ከዚህ እንቅስቃሴ መሪዎች መካከል የነበሩ አንዱ፣ ዶክተር ሞሐመድ አልባራዴ ይባላሉ። በተባበሩት መንግሥታት የዓለም አቀፍ ኑክሊያር ኤጀንሲ ሰብሳቢ ሆነው ለበርካታ ዓመት ያገለገሉ የተከበሩ ሰው ናቸው። እንደ ሳዳም ሁሴን የመሳሰሉ ሽብርተኛ መንግሥታት፣ ጅምላ ጨራሽ መሣሪያዎች በማከማቸት ለዓለም ስጋት እንዳይፈጥሩ፣ የታገሉ የሰላም ሰው ናቸው። እኝህ ሰውና የሚመሩት ድርጅታቸው፣ እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ2005 ዓ.ም. የሰላም ኖቤል ተሸላሚ ሆነዋል። ታዲያ ሰላማዊ በሆነ መልኩ፣ አምባገነኑ የሙባረክ መንግሥት ለሕዝብ ፍቃድ ተጠያቂ እንዲሆን፣ የሥርዓት ለውጥ እንዲመጣ፣ መታገላቸው፣ እኝህን የሰላም የኖቤል ተሸላሚ፣ ሽብርተኛ ያሰኛቸዋልን?
ከሰባት ወራት በፊት ጆን ኬሪ፣ ሃርድ ቶክ ቢቢሲ ባዘጋጀው ዝግጅት ላይ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተማሪዎች ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሰጥተው ነበር። ጆን ኬሪ ንግግራቸውን ሲጀመሩ የተናገሩትን ማንሳት እፈልጋለሁ። በግብጽ ስለነበረው፣ ህወሓት/ኢሕአዴግ ሽብርተኝነት ብሎ ስለሚጠራው፣ እንቅስቃሴ የሚከተለውን ነበር ያሉት፡
"... the greatest concern has to be the lack of the fulfillment by governments in many countries, of the aspirations of people. Particularly the creation of jobs, and the educational opportunities that are needed, for this modern world ... In Egypt, that was not a revolution that was moved by Islamism, or any ideology ... It was young people ... it was you ... people who came to the square, and twitted each other, texted each other, e-mail each other and brought people ..."

ጆን ኬሪ፣ በግብጽ የታየውን ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንደ ትልቅ ምሳሌ አጉልተው፣ እስክንደር ነጋና ሌሎች ከተናገሩት አባባሎች ጋር የሚስማማ ንግግር ሲናገሩ፣ የህወሓት/ኢሕአዴጉ ዶ/ር ቴዎድሮስ ቁጭ ብለው ያዳምጡ ነበር። ታዲያ ጆን ኬሪ፣ የግብጽን እንቅስቃሴ በመደገፋቸው፣ የአፍሪካ ወጣቶች ከግብጽ ወጣቶች እንዲማሩ በማባረታታቸው፣ ሽብርተኛ ሆኑን?
በግብጽ የታየው "አምባገነኖችን እምቢ የማለት ሰላማዊ እንቅስቃሴ፣ ዓለም አቀፍ ሕግን ያከበረ፣ በሰለጠነው ዓለም አድናቆትን ያተረፈ፣ የሕዝብ ጉልበት ታፎኖ እንጂ፣ ቢነሳ፣ ተዓምር ሊያደርግ እንደሚቻል ያስተማረ፣ ለአምባገነኖች ፍርሃትን የለቀቀ እንቅስቃሴ ነው። ሽብርተኝነት በፍፁም ሊሆን አይችልም።
ሌላው ማንሳት የምፈልገው፣ አቶ ብርሃኑ፣ ከየት ዘለው እስክንደር ነጋን ከግንቦት ሰባት ጋር እንዳገናኙት ነው። በግብጽ የነበረው ሰላማዊ እንቅስቃሴ ነው። ግንቦት ሰባት "የሰላም እንቅስቃሴ አይሠራም። ስለዚህ ነፍጥ ጨብጫለሁ" ያለ ደርጅት ነው። እንዴት ተደርጎ ነው፣ ታዲያ፣ በግብጽ የታየውን ሰላማዊ እንቅስቅሴ መደገፍ፣ የግንቦት ሰባት አባል የሚያሰኘው? እዚህ ላይ ህወሓት/ኢሕአዴጎች እራሳቸውን ያስገመቱ ይመስለኛል።
እንግዲህ የህወሓት/ኢሕአዴግ ባለሥልጣናትን የምመክረው ቆም ብለው እንዲያስቡ ነው። እያራመዱት ያለው ፖለቲክ የማያዋጣ የኋላ ቀር ፖለቲካ ነው። ዜጎችን በማሰርና ዜጎችን በማፈን የሚገኝ ቅንጣት ያህል ጥቅም የለም። ከጊዜ ወደ ጊዜ ከሕዝቡ ጋር መቃቃሩን ማቆም አለባቸው። የታሰሩ የሕሊና እሥረኞችን በሙሉ ይፈቱ ዘንድ፣ ሽብርተኝነት እያሉ ሕዝቡን ማሸበር ያቆሙ ዘንድ፣ ሀገር ቤት ካሉ በሕግ ከተመዘገቡ ሰላማዊ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር፣ የፖለቲካ ምኅዳሩን በማስፋትና የዴሞክራሲ ተቋማትን በማሻሻሉ አንጻር ይመካከሩ ዘንድ፣ የዘጓቸው ጋዜጦችን ይከፍቱ ዘንድ በአክብሮት እጠይቃለሁ።



